1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አርዲ፣ የሰዉ ዘር የቅም ቅም አያት

ሐሙስ፣ ጥቅምት 19 2002

ኢትዮጽያ ዉስጥ የዛሪ 17 አመት የተገኘው ቅሪተ አጽም ስለ ሰዉ ልጅ አመጣጥ ታሪክ የነበረዉን እምነት ማስለወጡን የቅሪተ አካል ተመራማሪዎች አስታዉቀዋል።

https://p.dw.com/p/K45g
4.4 እድሜ ያላት አርዲምስል picture alliance / dpa

የዛሪ አስራ ሰባት አመት ግድም በአዋሽ ሸለቆ የተገኘዉ የሴት ቅሪተ አጽም አርዲ የሚባል መጠሪያ ሲሰጠዉ፣ እንደ ሉሲ የሰዉ ልጅ የጽም ቅርጽ ሙሉ በሙሉ ባይኖዉም ሉሲን ግን አንድ ነጥብ አንድ ሚሊዮን አመት እንደ ሚበልጥ ተገልጸዋል።

የሉሲንም ሆነ የአርዲን ቅሪተ አጽም ከአለም አቀፍ ተመራማሪዎች ጋር በመሆን ጥናት ሲያደርጉ የቆዩት ዶክተር ዮሃንስ ዘለቀ አዲስ ስለተገኘዉ እጅግ ጥንታዊ ቅሪተ አጽም ጉዳይ እንዲያጫዉቱን ጋብዘናል።
በአሜሪካን ዋሽንግተን ዲሲ በአሜሪካን የተፈጥሮ ሳይንስ ሙዝየም አባል እና ረዳት ፕሮፊሰር ዮሃንስ ዘለቀ፣ የዛሪ 35 አመት ሉሲ ስትገኝ ከአለም ምሁራን ጋር በመሆን በግኝቱ ላይ ምርምር አድርገዋል። አሁንም አርዲ የተሰኘዉ ቅሪተ አጽም ከተገኘ በኻላ ከምሁራን ጋር በመሆን ምርምር ላይ መሆናቸዉን ይገልጻሉ። ሰሞኑን ለአለም ህዝብ ይፋ ስለሆነዉ ስለጥንታዊዉ ቅሪተ አጽም ጉዳይ ምን ይላሉ ስንል ነበር ጥያቄያችንን የጀመርነዉ «ይህ ግኝት ባለፉት 15 አመታት ከፍተኛ ጥናት ሲደረግበት የከረመ ጉዳይ ነዉ። አሁን በቅርቡ ሳይንስ በተባለዉ መጽሄት አፋር ዉስጥ በጆግራፊ በአፈር ጥናት እና ምርምር እንዲሁም በከባቢ ሁኔታ ጥናት ላይ ዘገባ ቀርቦአል። ይህ Ardipithecus ramidus የተባለዉ ቀደም ሲል እ.አ 1991 አ.ም የተገኘዉን ዝርያ ለማወቅ የተደረገ ጥረት ሲሆን ከቺንፓንዚ መሰልነት ዘር ወጣ ያለ ትክክለኛ የሰዉ ዘር ሃረግ ግንድ ላይ ያለ ነዉ ተብሎአል። ምንም እንኻ ቅሪተ አጽሙ የዛሪ 17 አመት ቢገኝም የምርምሩ ስራ በደንብ ከስር መሰረቱ ሲካሄድ እና ግኝቱ ለአለም ህዝብ ይፋ እስኪ ሆን ይህን ያህል እድሜና ግዜ ወስዶአል። ዶክተር ዮሃንስ በመቀጠል ይህ ጥናት፣ ሰዉ ከየትኛዉ ዝርያ ነዉ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣዉ፣ ምን ነበር ብሎ ለመተንተን በአዋሽ ሸለቆ የተገኘዉ ቅሪተ አጽም ይበልጥ በግልጽ የሚያሳይ ነዉ ሲሉ አክለዋል። የመጀመርያዉ ዝርያ የዛሪ 4.4 ሚሊዮን አመት በፊት በግሩ ቆሞ መሄድ የቻለ እንስሳ ወይም ሰዉ መሰል ዝርያ ያለዉ ነዉ። አርዲ ከሉሲ ቅሪተ አጽም የሚለየዉ አንደኛ በ 1.2 ሚሊዮን እድሚ ሊሲን በመብለጡ እደሆነ የሚገልጹት ዶክተር ዮሃንስ በሁለተኛነት የሉሲ ቅሪተ አጽም ከሰዉ የሚለያት በጣም በጥቂት ሁኔታ ነዉ ብለዋል። አርዲ በአገጭ አጥንቶችዋ፣ በዝንጀሮ እና በሰዉ መካከል ያለ ሁኔታን ሲያመለክት ግን በጣም ወደ ሰዉ ዝርያ ማለት ወደ ሉሲ ዝርያ ሲጠጋ ሌላዉ የእግር የእጅ አጥንቶች ዛፍ ላይ ለመንጠልጠል የሚረዳ አይነት በመሆኑ ከሉሲ ይለያታል ብለዋል። እናም ይላሉ በመቀጠል ዶክተር ዮሃንስ በሉሲ እና በአርዲ መካከል ያለዉን ልዩነት ስናይ በመካከላቸዉ የአዝጋሚ ለዉጥ እንዳለ በግልጽ እናያለን።
ይህም ግኝት ኢትዮጽያችን የሰዉ ዘር መገኛ መሆንዋን ያሳየናል የሚሉት ዶክተር ዮሃንስ ዘለቀ፣ በኢትዮጽያ በተለይ በአዋሽ ሸለቆ አካባቢ ሁሉም አይነት ዝርያዎች በአካባቢዉ ባለዉ ጽዱ የሆነ አፈር አይነት፣ ማለት አፈሩ አሲድ የሌለዉ በመሆኑ ወይም በጣም አነስተኛ አሲድነት ስላለዉ ይህ አይነቱ ቅሪተ አጽም ተጠብቆ ቆይቶአል፣ በዚህም ኢትዮጽያችን ልዩ ሆና ትገኛለች ሲሉ ገልጸዋል። ኢትዮጽያ ለአለም ህዝብ እጅግ ጥንታዊ የሆነ መረጃ በማቅረብ ተቀዳሚ ቦታን ይዛለች በማለትም አክለዋል።
ቅሪተ አጽሙ አርዲ የሚል መጠርያ የተሰጠዉ ይህ ቅሪት አጽም በሚገኝበት አካባቢ የሚኖሩ ህዝቦች በሚናገሩበት በአፍር ቋንቋ ሲሆን አርዲ ማለት በአፋርኛ መሪት ማለት ሲሆን፣ ራሚስ ማለት ደግሞ በአካባቢዉ የሚገኘዉ የወንዝ መጠርያ መሆኑን ገልጸዋል። አርዲ የተሰኘዉ የአነስታይ ጾታ ጥንታዊ ቅሪተ አጽም በኢትዮጽያ ብሄራዊ ሙዝየም ሲገኝ፣ ይህ ቅሪተ አጽም አንድ ብቻ እንዳልሆነ የገለጹት ዶክተር ዮሃንስ ያልተምዋላ የተለያዩ የሰዉንነት ክፍለ አጥንቶች ከዚሁ ከአርዲ ቅሪተ አጽም ጋር እንደተገኙ በማከል ገልጸዋል።
ኢትዮጽያ ማለት በግሪክ ቋንቋ ጥቁር ማለት ነዉ ሲሉ የሚገልጹት ዶክተር ዮሃንስ ዘለቀ፣ ከዚህ ጥቁር አፈር የተፈጠረ የአለም ህዝብ፣ አያት ቅድመ አያት፣ የቅም ቅም አያት፣ ኢትዮጽያ ናት። ይህ ሲባል አፍሪቃችን፣ ኢትዮጽያችን የሰዉን ልጅ ታሪክ የያዘች ማህደር ስትሆን እንደ ፒራሚድ እንደ ላሊበላ እንደ አክሱም ያሉ ጥንታዊ ቅርጾች የሚገኙባት የአለም ታሪክ ማህደር በመሆን በተለይ ደግሞ አሁን አርዲ የኢትዮጽያን በሰፊዉ ለአለም ህዝብ ለማስተዋወቅ ከፍተኛ መረጃ በመሆን መቅረቧን ኩራት ነዉ ሲሉ ገልጸዋል።

Ardi revolutioniert Bild unserer frühen Vorfahren
ምስል picture alliance / dpa

አዜብ ታደሰ