1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኮሌራ 15 ገደለ፣800 ለከፈ

ዓርብ፣ ግንቦት 4 2015

የክልሉ የህብረተሰብ ጤና ተቋም እንዳለዉ በሽታዉ በክልሉ አምስት ዞኖችና በሶስት ልዩ ዞኖች ተሰራጭቷል።የጤና ተቋሙ እንደሚለዉ የበሽታዉን ስርጭት ለመቆጣጠር እየጣረ ነዉ

https://p.dw.com/p/4RHJi
Mosambik | Cholera Ausbruch
ምስል Sitoi Lutxeque/DW

የደቡብ ኢትዮጵያ የኮሌራ በሽታ

መረጃዎች እንደሚጠቁሙት በደቡብ ክልል የተከሰተው የኮሌራ በሽታ ባለፈው ወር አጋማሽ ለመጀመሪያ ጊዜ የታያው በክልሉ ጌዲኦ ዞን ወናጎ ወረዳ ውስጥ ነበር ፡፡ አሁን ላይ በሽታው  በክልሉ አምስት ዞኖችና ሦስት ልዩ ወረዳዎችን መዳረሱን የደቡብ ክልል የህብረተሰብ  ጤና ተቋም አስታውቋል ፡፡

ጌዲኦ ፣ጋሞ ፣ ጎፋ ፣ ደቡብ ኦሞ ፣ ኮንሶ  ዞኖችና እንዲሁም አማሮ ፣ ቡርጂ እና አሌ ልዩ ወረዳዎች በሽታው የታየባቸው ናቸው ፡፡በእነኝሁ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች እስከአሁን 15 ሰዎች መሞታቸውንና ከ800 በላይ የሚሆኑት ደግሞ መታመማቸውን  የተቋሙ የበሽታ መከላከል ከፍተኛ ባለሙያ አቶ ታሪኩ መለሰ ለዶቼ ቬለ DW  ገልጸዋል

አሁን ላይ በበሽታው ለታመሙ ሰዎች ህክምና መሰጠቱን የጠቀሱት አቶ ታሪኩ “ በተለይም በጤና ተቋማት የጋጠመውን የህክምና አሰጠጥ ጥራት ችግር ለመቅረፍ እየተሠራ ይገኛል ፡፡ እንዲሁም በሽታው በተከሰተባቸው ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ለሚገኙ የጤና ባለሙያዎች በኮሌራ ህክምና ላይ ያተኮረ የሥራ ላይ ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ በአሁኑወቅትም በሽታው ወደ ሌሎች አካባቢዎች እንዳይስፋፋና አሁን በተከሰተባቸው አምስት ዞኖችና ሦስት ልዩ ወረዳዎች ውስጥም ተጨማሪ ጉዳት እንዳያደርስ ትምህርት ቤቶችና የገበያ ሥፍራዎችን ጨምሮ ህዝብ በብዛት በሚገኝባቸው አካባቢዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ በመከናወን ላይ ይገኛል “ ብለዋል፡፡

Mikroskopaufnahme von Cholera Bakterien
ምስል Callista Images/IMAGO

የኮሌራ በሽታን የመከላከሉ ሥራ የሁሉንም ድጋፍና  የቅንጅት ሥራን እንደሚጠይቅ  የሚናገሩት የክልሉ ህብረተሰብ  ጤና ተቋም የበሽታ መከላከል  ከፍተኛ ባለሙያው አቶ ታሪኩ መለሰ ለዚህም በጤናው ዘርፍ ላይ በሚሠሩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች በኩል የተጀመረው  ውስን ድጋፍ ከፍ ሊል ይገባል ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያ የበጋው ወቅት ማብቃቱን ተከትሎ እየጣለ ከሚገኘው ዝናብ ጋር በተያያዘ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የኮሌራ እና የኩፍኝ በሽታዎች መከሰታቸውን የጤና ሚኒስቴር ባለፈው ወር መግቢያ ላይ ማስታወቁ አይዘነጋም ፡፡ የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ እርዳታ ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በበኩሉ በኢትዮጵያ ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ በተከሰተ የኮሌራ በሽታ 84 ሰዎች ሲሞቱ ከ 5 ሺህ በላይ የሚሆኑት መታመማቸውን ባለፈው ሳምንት ባወጣው ሪፖርት ይፋ ማድረጉ ይታወቃል፡፡

ሸዋንግዛዉ ወጋየሁ 

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሰ