1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያ፣የባሕር በር የማግኘት ጥረቷ እና የሀገራት ምላሽ

ሰኞ፣ ጥር 13 2016

ኢትዮጵያ ከራስ ገዟ ሶማሊላንድ ጋር በቅርቡ የተፈራረመችው የመግባቢያ ስምምነት የባሕር በር ማግኘት የምትችልበት የትብብርና የአጋርነት ስምምነት መሆኑ ሊታወቅ እንደሚገባ አስታወቀች። ኢትዮጵያ ይህን ያለችው የግብፁ ፕሬዝዳንት አል ሲሲ ሀገራቸው የትኛውም ሀገር ሶማሊያንም ሆነ ደኅንነቷን ስጋት ውስጥ እንዲጥል አትፈቅድም ማለታቸውን ተከትሎ ነው።

https://p.dw.com/p/4bXbw
Äthiopien Unterzeichnung des Memorandum of Understanding zwischen Ethiopia and Somaliland
ምስል TIKSA NEGERI/REUTERS

ኢትዮጵያ፣የባሕር በር የማግኘት ጥረቷ እና የሀገራት ምላሽ

የግብጽ ክስ እና ዛቻ በኢትዮጵያ ላይ 

የጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ የብሔራዊ ደህንነት አማካሪ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ትናንት በ ኤክስ መገናኛ ዐውታር ባሰፈሩት ጽሑፍ ፣ ሶማሊያ አስቸጋሪ ጊዜ ውስጥ በነበረችበት ወቅት ከጎኗ ያልነበሩ ያሏቸው አካላት ዛሬ ደጋፊዋ ሆነው የመጡበት ምክንያት ኢትዮጵያን ከመጥላት የሚነሳ ነው። ኢትዮጵያ ከሳምንታት በፊት ከራስ ገዟ ሶማሊላንድ ጋር የተፈራረመችው የመግባቢያ ስምምነት የባሕር በር ማግኘት የሚያስችላት "የትብብርና አጋርነት ስምምነት እንጂ ግዛት መጠቅለል ወይም ሉዓላዊነትን በሌላ አገር ግዛት ላይ ማወጅ አይደለም" ሲሉ ተናግረዋል። 

አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የደኅንነት አማካሪ
አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የደኅንነት አማካሪ ምስል Minasse Wondimu Hailu/AA/picture alliance

አምባሳደር ሬድዋን ይህንን ያሉት የግብፁ ፕሬዝዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ ከሶማሊያው አቻቸው ጋር በካይሮ ከተወያዩ በኋላ በሰጡት መግለጫ ሀገራቸው የትኛውም ሀገር ሶማሊያንም ሆነ ደኅንነቷን ስጋት ውስጥ እንዲጥል አትፈቅድም ማለታቸውን ተከትሎ ነው። 


የኢጋድ የመሪዎች አስቸኳይ ጉባኤ ሐሙስ በኢትዮጵያ እና ሶማሊያ ውዝግብ ላይ ይመክራልግብፁ ኢትዮጵያ የባሕር በር ለማግኘት ከሶማሊላንድ ጋር ያደረገችውን ስምምነት ግዛትን በኃይል የመቆጣጠር ሙከራ እድርጋ ከዚህ በፊትም በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ በኩል ገልጻለች። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል ዐቀባይ አምበሳደር መለስ አለም በሳምንቱ መጨረሻ በሰጡት መግለጫ ግብጽ ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር የተፈራረመችውን የባሕር በር የሚያስገኝላትን የመግባቢያ ስምምነት ተከትሎ ኢትዮጵያን የአካባቢው አለመረጋጋት መንስኤ አድርጋ መክሰሷን ገልፀው ነበር።

Abdel Fattah el-Sisi - Hassan Sheikh Mohamud meeting in Cairo
ምስል Somalian Presidency/Anadolu/picture alliance

ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተያያዘ መንግሥት ከሶማሊላንድ ጋር የተፈራረመውን የመግባቢያ ስምምነት "መልሶ ሊያጤነው ይግባል" ሲል እናት ፓርቲ ባወጣው መግለጫ ጠይቋል።አነጋጋሪነቱ የቀጠለው የወደብ ጉዳይ
ፓርቲው ይህንን ያለው ጉዳዩ ኢትዮጵያን ከሶማሊያ ፣ ከአፍሪካ ሀገራት እና ከአለም አቀፉ ማህበረሰብ ጋር ውጥረት እና ግጭቶች ውስጥ እንዳይከታት እና በሶማሌ ክልል ሌላ ጥያቄና ቀውስ እንዳይፈጥር ሥጋት ስላለው መሆኑን ገልጿል። የፖርቲው የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዳዊት ብርሃኑን ፓርቲው መንግሥትን ስምምነቱን መልሶ ያጢን ሲል ምን ማለቱ እንደሆን ጠይቀናቸዋል።

የምክር ቤቱ መግለጫ አይወክለንም ፤ ሁለቱ ፓርቲዎች

ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ ስምምነቱ የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ ተቀባይነት ችግር ውስጥ የሚከት መሆኑን በመግለጽ በዘጠኝ ነጥቦች ምክንያት ስምምነቱን እንደሚቃወመው አስታውቋል። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት በበኩሉ ለስምምነቱ ውጤታማነት በጋራ በመቆም ሚናችንን ለመወጣት ያለንን ቁርጠኝነት እናረጋግጣለን በማለት ስምምነቱን መደገፉ ይታወሳል። ሁለቱ ፓርቱዎች ይህ የጋራ ምክር ቤቱ መግለጫ እንደማይወክላቸው ገልፀዋል።የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አቋም ሶማሊያ የሉዓላዊ ግዛቷ አካል አድርጋ ከምትቆጥራት ሶማሌላንድ ጋር ኢትዮጵያ ያደረገችው ስምምነት የቃጣናው ዐቢይ አለምአቀፍ ጉዳይ ሆኖ ቀጥሏል። ለኢትዮጵያ ወታደራዊ እና የንግድ እንቅስቃሴ ለማከናወን የሚያስችላትን የባሕር በር የሚያስገኝላት ነው የተባለው ስምምነት ከተፈረመ ከአንድ ወር በኋላ ሂደቱ ተጠናቆ ወደ ሥራ እንደሚገባ መግባባት ላይ መደረሱ በስምምነቱ ወቅት ተገልጾ ነበር። 

ሰሎሞን ሙጬ
ኂሩት መለሰ