1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ጋምቤላ ዉስጥ ታጣቂዎች በከፈቱት ጥቃት ሰዎች ገደሉ

ማክሰኞ፣ መጋቢት 17 2016

በጋምቤላ ክልል አኙዋ ብሔረሰብ ዞን አቦቦ ወረዳ ውስጥ የታጠቁ ሐይሎች ባደረሱት ጥቃት ከሶስት በላይ ሰዎች መገደላቸውን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው ማንነታቸው በውል ያልታወቁ ታጣቂዎች በተለያዩ ወቅቶች ግዲያ እንደሚፈጽሙ የተናገሩት ነዋሪዎቹ ትናንት የተገደሉትም ሰዎች በአንድ የእርሻ ኢንቨስትመንት አካባቢ ነው።

https://p.dw.com/p/4e8HJ
Äthiopien Straßenszene aus Gambela
ምስል Privat

በጋምቤላው የታጣቂዎች ጥቃት በትንሹ ሶስት ሰዎች ተገድለዋል

በአኙዋ ብሔረሰብ ዞን አቦቦ ወረዳ ታጣቂዎች በሰላማዊ ሰዎች ላይ ጥቃት አደረሱ

በጋምቤላ ክልል አኙዋ ብሔረሰብ ዞን አቦቦ ወረዳ ውስጥ የታጠቁ ሐይሎች ባደረሱት ጥቃት ከሶስት በላይ ሰዎች መገደላቸውን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው ማንነታቸው በውል ያልታወቁ ታጣቂዎች በተለያዩ ወቅቶች ግዲያ እንደሚፈጽሙ የተናገሩት ነዋሪዎቹ ትናንት የተገደሉትም ሰዎች በአንድ ኢንቨስትመንት እርሻ አካባቢ እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ ያነጋርናቸው ነዋሪዎች በጥቃቱ ህይወታቸው ያለፈው ሰዎች ቁጥር አስመልክቶ የተለያዩ አስተያየቶች ሰጥቷል፡፡ አንድ ነዋሪ በጥቃቱ አምስት ሰዎች ህይወት ማለፉን የገለጹ ሲሆን ሌላው ደግሞ ሶስት ሰዎች መሞታቸውን ጠቁመዋል፡፡የጋምቤላ ክልል ፀጥታ ከአደባባይ ተኩስ በኋላ

አንድ የፖሊስ አባል ደግሞ በስፍራው በደረሰው ጥቃት 4 ሰዎች ህይወት ማለፉንና አንድ ሰው ደግሞ ቆስሎ ሆስፒታል መግባቱን ተናግረዋል፡፡ በጉዳዩ ከሚመለከታቸው የመንግስት ስራ ኃላፊዎች መረጃ ለማግኘት ዶይቼ ቬለ ያደረገው ተደጋጋሚ ጥረት ስልክ ባለመነሳቱ አልተሳካም፡፡

በከብት ጥበቃ ላይ የነበሩ ሰዎች ህይወት አልፏል 

በአኙዋ ብሔረሰብ ዞን አቦቦ ወረዳ  የታጠቁ ሀይሎች ባደረሱት ጥቃት በከብት ጥበቃ ላይ  የነበሩ  ሰዎች ህይወት ማለፉን ያነጋገርናቸው አንድ ነዋሪ ተናግረዋል፡፡ ስሜ አይገለጽ ያሉ ነዋሪ በሰጡን አስተያየት በታጣቂዎቹ ጥቃት ከደረሰባቸው ሰዎች መካከል ሁለት ሰዎች በአንድ ስፍራ ጥቃት እንዳደረሱባቸው እና 3ቱ ደግሞ በአንድ እርሻ ኢንቨስትመንት አካባቢ ከብት በመጠበቅ ላይ የነበሩ ሰዎች እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡ በሰዎች ላይ ከደረሰው ጉዳት በተጨማሪ 8 ያህል ከብቶች በጥቃት አድራሾች መወሰዳቸውን ነዋሪው አክለዋል፡፡የጋምቤላ እና ደቡብ ምዕራብ ኢትየጵያ ክልሎች የሠላም እና ልማት ትብብር መሰረቱ

ከአቦቦ ወረዳ አስተያየታቸውን የሰጡን ሌላው ነዋሪም በአካባቢው በደረሰው ጥቃት ሶስት ሰዎች ህይወት ማለፉን እንደሚያውቁና በቦታው  ማየታቸውን  ተናግረዋል፡፡ ጥቃት ከደረሰባቸው መካከል በዓመት አንድ ጊዜ ለከብት ግጦሽ ወደ አካባቢው የሚመጡ አርብኛ ተናጋሪ የሌላ ሀገር ዜጎች  እንደሚገኙበት ገልጸዋል፡፡  በወረዳው አርብቶ አደሩ ከቦታ ቦታ ከብቶቻቸውን ይዞ ሲንቀሳቀሱ ተደጋጋሚ ጥቃቶች በአካባቢው በሚንቀሳቀሱ ሽፍቶች እንደሚደርስባቸው አመልክተዋል፡፡ በእዚህ አካባቢ ከዚህ ቀደምም የታጠቁ ቡድኖች በተደራጀ መልኩ ወደ መንደር በመግባት በሰው ላይ ጥቃት በማድረስ የቁም እንስሳት ዘርፎ እንደነበር አመልክተዋል፡፡

በጋምቤላ ክልል አቦቦ ወረዳ የደረሰው ጉዳት አስመልክቶ ማብራሪያ ለመጠየቅ ወደ ክልሉ ኮሙኒኬሽን ጉዳዩች ጽህፈት ቤት ተደጋጋሚ ያደረኩት የስልክ ሙከራዎች አልተሳኩም፡፡ የክልሉ የፀጥታ ሁኔታ ላይ የፌዴራልና የክልል የፀጥታ አካላት የተሳተፉበት የዉይይት መድረክ  በጋምቤላ ከተማ እየተካሄድ እንደሚገኝ የክልሉ ኮሙኒኬሽን በማህበራዊ ትስስር ገጹ አመልክተዋል፡፡በጋምቤላ ክልል አቦቦ ወረዳ በደረሰው ጥቃት የአራት ሰዎች ሕይወት ማለፉ

በታህሳስ 2016 ዓ.ም በአቦቦ ወረዳ መንደር 17 ተብሎ በሚታወቅ አካባቢም ያልታወቁ የተባሉ ሀይሎች ባደረሱት ጥቃት የአራት ሰዎች ህይወት ማለፉን  መዘገቡ ይታወሳል፡፡ በጋምቤላ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በሚደርሱት ግጭቶችና ጥቃቶች በሰዎች ህይወት እና ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት  መድረሱ በተደጋጋሚ ተዘግቧል፡፡

ነጋሳ ደሳለኝ

ታምራት ዲንሳ

ማንተጋፍቶት ስለሺ